31/05/2024
የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ተመላከተ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማህበረሰቡን ከልማት ትሩፋቶች ተጠቃሚ ለማድረግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ተመላክቷል።
የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በክልሉ ፋይናንስ ቢሮ የፋይናንስ ኃብት አስተዳደር ዘርፍ ላይ ምልከታ አድርጓል።
በክልሉ በያዝነው ዓመት ተገንብተው በመጠናቀቅ ላይ የሚገኙ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የመስኖ፣ የገጠር ሴፊቲኔት የችግኝ ጣቢያዎችና የኮሪደር ልማት ሥራዎች ምልከታ ተደርጎባቸዋል።
በክልሉ ተገንብተው በከፊል አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ የውሃ መሠረተ ልማት ሥራዎች ተጎብኝተዋል።
በክልሉ በመገንባት ላይ ከሚገኙ ከ400 በላይ የግንባታ ፕሮጀክቶች ውስጥ 87ቱ በያዝነው ዓመት ይጠናቀቃሉ ተብሏል።
የክልሉ የፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ የመደበኛ በጀት አፈፃፀም 79 በመቶ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በጀትን በተዘጋጀው ቀመር መሠረት ለሁሉም ዞኖችና እስከታችኛው መዋቅር በወቅቱ ተደራሽ በማድረግ ላይ እንገኛለን ብለዋል።
የሚከናወኑ ኘሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜና በጀት ለማጠናቀቅ በመሥራት ላይ እንገኛለን ያሉ ሲሆን ክልሉ አዲስ ከመሆኑ ጋር ተዳምሮ የበጀት ዕጥረት መኖሩን ገልፀዋል።
ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ ለማጠናቀቅ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የቋሚ ኮሚቴው ቡድን መሪ የተከበሩ ዶ/ር ሚኪያስ አየለ ገልጸዋል።
በጀትን ለታለመለት ዓለማ በማዋል የህዝብን የልማት ፍላጎት ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት የሚበረታታ ነው ብለዋል።
በክልሉ የሚገኙ አማራጭ የፋይናንስ ምንጮችን ማስፋት፤ ባለኃብቶችና ማህበረሰቡን የልማት ሥራዎች ተሳታፊ ማድረግ እንደሚገባ ቋሚ ኮሚቴው አመላክቷል።
ተጠናቀው ወደ አገልግሎት ያልገቡ ፕሮጀክቶች የማህበረሰቡ የቅሬታ ምንጭ እንዳይሆኑ ወደ አገልግሎት ሊገቡ እንደሚገባ ተመልክቷል።
የፋይናንስ ብክነትን ለማስቀረት የተዘጋጁ አሰራሮችና መመሪያዎች አበረታች ናቸው ተብሏል።
አዳዲስና ዘመናዊ የግዥና የፋይናንስ ስርዓቶች ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ እንዲሁም ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግና ወደ አመራርነት ማምጣት ላይ ትኩረት እንዲደረግ ቋሚ ኮሚቴው አሳስቧል።
ምንጭ ፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት
