13/03/2017
በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሴክተር ልማት ጥናትና ምርምር ዳይሬክቶሬት በሴክተሩ ለውጥ ሊያመጡ የሚችሉ ትላልቅ ፋይዳ ያላቸው ዘርፍ ዘለል የጥናትና ምርምር ሥራዎችን ለማከናወን ከትምህርትና ምርምር ተቋማት ጋር በጋራ ለመሥራት ትኩረት ያደርጋል፡፡
በሴክተሩ የጥናትና ምርምር ሥራ አፈጻጸም ላይ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በአጠቃላይ ስልቶች ላይ ለመወያየትና ለችግሮች መፍትሔ ለመፈለግ እንዲሁም በጀት የሴክተሩን የጥናትና ምርምር ሥራ ግብ ለማሳካት በተዘጋጁ ዕቅዶች ላይ በመነጋገር የአፈጻጸም ፕሮፖዛል ተዘጋጅቷል፡፡
በተጨማሪም ለሴክተሩ ጥናትና ምርምር ሥራ አፈጻጸም ሀገራዊ የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ በመወያየት ግብአት የተሰባሰበ ሲሆን ከዩኒቨርስቲዎች ጋር ትስስርን ለማጠናከር ቀጠናዊ አደረጃጀቶችን ለማቋቋም እና ሴክተሩን የጥናት ምርምር ሥራ በቅንጅት ለመስራት የጋራ መግባባትን መፍጠር ያስቻለ የምክክር መድረክ ከጥር 2-4/2009 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ጌትፋም ሆቴል ተካሂዷል፡፡
09/03/2017
በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሴክተር ልማት፣ጥናትና ምርምር ዳይሬክቶሬት ከ2008 ዓ.ም አጋማሽ ጀምሮ የተቋቋመ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህም መሠረት በዳይሬክቶሬቱ 11 የሚደርሱ ባለሙያዎች የተቀጠሩ ሲሆን ባለሙያዎችም አዲስ እንደመሆናቸው መጠን የስራ አፈጻጸም ተልዕኮ እና የ2ዐዐ9 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከጥቅምት -/፻፱ ዓ.ም በኢትዮጵያ ሆቴል ለሁለት ቀናት በተሰጠው ስልጠና፡፡በዳይሬክቶሬቱ ዳይሬክተር አቶ ተፈሪ ተክሉ በዳይሬክቶሬቱ አደረጃጀትና መዋቅር ላይ ገለጻ ካአደረጉ በኋላ አቶ ሙሉጌታ ክንፌ የሚኒስቲር መስራያ ቤት የሰው ሀበት ልማትና አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ስልጠናውን አስጀምረዋል፡፡
በቢ.ፒ.አር፣ ቢ.ኤስ.ሲን እንዲሁም ስለ ስራ አፈጻጸም ምዘና አስመልክቶ የለውጥና የመልካም አስተዳደር ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት አቶ ተስፋዓለም ታደሰ ስልጠና ሰጥተዋል፡፡ አቶ አስቻለው ፍቅሬ የሚ/ር መሥሪያ ቤቱ የሰው ኃብት ልማትና አስተዳደር ባለሙያ ስለ የመንግስት ሠራተኛ መብትና ግዴታ፣ ስለ እድገትና ዝውውር በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ስልጠና ሰጥተዋል፡፡አቶ ደስታ ሎሬንሶ በዳይሬክቶሬቱ የማይዳሰሱ ባህላዊ ሀብቶች ልማት ጥናት ምርምር ከፍተኛ ባለሙያ የዳይሬክቶሬቱን የ2ዐዐ9 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ የውይይት መነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል፡፡ ተሳታፊ የነበሩት የዳይሬክቶሬቱ ባለሙያዎች ከስልጠና በኋላ በቡድን በመሆን የዳይሬክቶሬቱን ዕቅድ በቢ.ፒ.አር እና ቢ.ኤስ.ሲ ስታንዳንድ መሠረት ተንትነው በማቀድ አቅርበዋል፡፡ በመጨረሻም ሰፋ ያለ ማብራሪያና አስተያየት ከተሳታፊዎች ተነስቶ ስልጠናው በስኬት ተጠናቋል፡፡
08/03/2017
አልነጃሽ ኢትዮጵያ ውስጥ በትግራይ ክልል ውቅሮ ከምትባል ከተማ በ10 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ፕላቶአማ በሆነ ቦታ የሚገኝ ታሪካዊ የመስህብ ቦታ ነው፡፡ አልነጃሺ ከመካ በመጡ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች አማካኝነት በ615 ዓ.ም ከእስልምና ሃይማኖት ጋር አብሮ የተመሰረ እንደሆነ ይነገራል ይህም ማለት በወቅቱ የነብዩ መሃመድ ተከተዮች የነበሩት በመካ በነበረው ችግር ምክንያት እምነታቸውን እንዳይተገብሩ ስለተከለከሉና እንግልት ስለደረሰባቸው በነብዩ መሀመድ ትእዛዝ መሰረት ወደ ኢትዪጵያ ብትሄዱ ተቀብሎ የሚያስተናግዳችሁ ንጉስ አለ ወደዛ ሂዱ እንዳላቸው የሚያስረዱ ታሪካዊ ድርሳናት አሉ ፡፡
ስያሜውንም ያገኘው ነጋሲ ከሚለው ቃል ሲሆን ቃሉም በአካባቢው ከሚነገረው የትግርኛ ቋንቋ ሲፈታ ትርጉሙ ንጉስ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሰረት ነጃሺ ወደ አረብኛ የተቀየረው ከዚህ ትርጓሜ እንደሆነ ይታመናል፡፡
በአሁኑ ወቅት ይህን ታሪካዊ የእምነት ቦታ ለማልማት TIKA በተሰኘ የቱርክ ግብረ ሰናይ ድርጅት ከክልሉ እስልምና ጉዳዩችና የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጋር በትብብር የተጀመሩ ስራዎች መኖራቸው ታውቋል፡፡ በተጨማሪም የክልሉ፣ የዞንና የወረዳ ባህልና ቱሪዝም ቢሮዎች ከህዝብ አደረጃጀቶች ጋር በመተባበር በአካባቢው ለሚኖረው ማህበረሰብ የማሳመንና የቅድመ ዝግጅት ስራ በክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ተሰርቷል፡፡
ይሁን እንጂ ቦታው ከእስልምና እምነት ጥንታዊ ታሪክ ጋር ቁርኝት ያለውን ያህል ታሪኩ ጎልቶ ካለመነገሩም በላይ ስፍራው ለጎብኝዎች በተፈለገው መጠን አልተዘጋጀም፡፡
በመሆኑም ከታሪካውያኑ እና ጥንታዊያኑ የዓለም እስልምና መካነ ቅርሶች ባልተናነሰ የጎብኝዎች ትኩረት አግኝቶ ለቱሪስት ተደራሽ ለማድረግ በቦታው ያሉ ተግዳሮቶችና መልካም አጋጣሚዎችን ለመለየት “አልነጃሽ ሲምፖዚም” በሚል የካቲት 18 እና 19 ታላቅ ሲምፖዚየም ተካሄዷል፡፡