06/06/2026
የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ አህጉራዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ ሊካሄድ ነው
በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን በተግባራዊ ፖሊሲዎች ለመደገፍ ያለመ አህጉራዊ ጉባኤ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰኔ 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል።
የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሲኤ) ያዘጋጀው ይህ ጉባኤ በአካዳሚክ ምርምሮች እና በፖሊሲ አፈጻጸሞች መካከል ያለውን ክፍተት መሙላትን ታሳቢ ያደረገ ነው።
የአፍሪካ ልማትና የተግባራዊ መፍትሄዎች መድረክ (ADIF 2026) የሚል ስያሜ ያለው ጉባኤ “በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ የሚረዱ ምርጥ ተሞክሮዎችና የፈጠራ መፍትሔዎች” በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄድ ነው።
ጉባኤው በአፍሪካ በፍጥነት እያደገ የሚገኘውን የወጣት ማኅበረሰብ፣ በዓመት ከ15 ሚሊዮን በላይ የሥራ ዕድል በመፍጠር አህጉራዊው ፍላጎትን ለመመለስ ከተያዘው ውጥን ጋር በቀጥታ የተገናኘ ነው።
ይህ አዲስ መድረክ ከተለመዱ አህጉራዊ ስብሰባዎች በተለየ፤ የፖሊሲ አፈጻጸምን በማፋጠን በዘርፉ ያለውን የፖሊሲ እና የአሰራር ሂደት ለማቀለጣፈ ያለመ መሆኑን ኢዜአ ከኢሲኤ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በዚህም መሠረት የኢኮኖሚክ ኮሚሽኑ በገንዘብ እጥረት ምክንያት መሬት ያልወረዱ ጥናታዊ ምርምሮችን ወደ ተግባር ለመለወጥ፣ በጥቂት አካባቢዎች ተሞክረው ስኬታማ የሆኑ አነስተኛ የሙከራ ፕሮጀክቶችን ለማስፋት እንዲሁም አህጉር በቀል ምርጥ ተሞክሮዎችን በአገራት አጠቃላይ የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች ውስጥ በቀጥታ ለማካተት አቅዷል።
አሠራሩ በልማት ላይ የሚፈሱ የአህጉሪቱ ኢንቨስትመንቶች አስተማማኝና ዘላቂ ውጤት እንዲያመጡ ለማድረግ ትልቅ እገዛ ይኖረዋል ተብሏል።
የፎረሙን ውጤታማነትና ተጠያቂነት በተረጋገጠ መልኩ ለመከታተልም፣ ከጉባኤው በፊት፣ በጉባኤው ወቅትና ከጉባኤው በኋላ የሚተገበር የአሠራር ሥርዓት ተዘርግቷል።
የመድረኩን ቀጣይነትና ትስስር አስተማማኝ ለማድረግ፣ የየዓመቱ መሪ ሀሳቦችን አንዱ ከሌላው ጋር በማስተሳሰር እና ተመጋጋቢ በማድረግ እንደሚዘጋጁ ኮሚሽኑ አስታውቋል።
በቀጣይ የሚካሄዱት ፎረሞች፤ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) ትግበራን ከአህጉራዊ የኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂዎች ጋር ማስተሳሰር ጨምሮ ሌሎች የልማት የትኩረት መስኮችን ታሳቢ በማድረግ እንደሚካሄድ መገለጹን ኢዜአ ዘግቧል።
05/06/2026
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ 5ኛ ዓመት 11ኛ መደበኛ ስብሰባ በዛሬው ዕለት አካሄደ።
ለካቢኔው በዛሬው በቀረቡ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን አስተላልፏል፡፡
በዚህ መሰረት፡-
1ኛ. የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ አስተዳደር ማቋቋሚያ ረቂቅ ደንብ ላይ ተወያይቶ ተፈፃሚ እንዲሆን አፅድቋል።
2ኛ. የመሬት ይዞታ ማስለቀቅና ካሳ ጉዳዮች ይግባኝ ሰሚ ጉባኤ እንደገና ማቋቋሚያ ረቂቅ ደንብ ላይ ተወያይቶ አፅድቋል።
3ኛ. በግል ዘርፍ ለህክምና ተቋማት ግንባታ እና ማስፉፍያ የሚውል መሬት ለማስተላለፍ የቀረበ የዉሳኔ ሀሳብ ላይ ተወያይቶ፣ ተፈፃሚ እንዲሆን አድፅድቋል።
05/06/2026
ጋዜጣዊ መግለጫ
ግንቦት 28 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ፡ ኢትዮጵያ
ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ
ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ማለዳ ላይ፤ የመጀመሪያው የወገግታ ጭላንጭል በከፍታማዎቹ የኢትዮጵያ ተራሮች ላይ ፈንጥቆ ጨለማውን ሳይቀድ በፊት ኢትዮጵያውያን ረጃጅም ሰልፍ ተሰልፈዋል። በጅማ፣ በድሬዳዋ፣ በሐዋሳ፣ በባሕር ዳር እንዲሁም ስማቸው በዓለም አቀፍ የዜና ጋዜጣዎች ላይ ፈጽሞ ሊወጣ በማይችሉ ከተሞችና መንደሮች ውስጥ ያሉ ወንዶችና ሴቶች፤ ወሳኝ ተግባር ለመፈጸም በሰልፍ ቆሙ። ድምፅ ሰጡ! ይህንን ታሪካዊ ኃላፊነት ለመወጣት ከሃምሳ አራት ሚልዮን በላይ የሚሆኑ ዜጎች ተመዝግበው ነበር። ይህ ቁጥር ከአንዳንድ ሀገሮች አጠቃላይ ሕዝብ ቁጥር በላይ ነው። ይህ ምርጫ እውነተኛ ስለመሆኑ ጥያቄ ለሚያነሣ ለማንኛውም አካል ግልጽ እና የማያሻማ ምላሽ ሰጥቷል!
የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍላጎት
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከ52,000 ምርጫ ጣቢያዎች መካከል ከ50,188 በላይ የሚሆኑት በሰዓቱ ተከፍተው ቀኑን ሙሉ መራጮችን ሲያስተናግዱ እንደነበር አረጋግጧል። ከ42 የፖለቲካ ፓርቲዎች የተወጣጡ ከ10,438 በላይ ዕጩዎች እና 80 የግል እጩዎች በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የክልል ምክር ቤት ወንበሮችን ለማሸነፍ ተወዳድረዋል። ይህ በማንኛውም ሊለካ በሚችል መሥፈርት በኢትዮጵያ ታሪክ ትልቁ እና በውሳኔ አሰጣጥም ሆነ በአስተዳደራዊ ረገድ እጅግ በረቀቀ ሁኔታ ተግባራዊ የተደረገ ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ የታየበት ኩነት ነበር።
የቀድሞው የኬንያ ፕሬዚዳንት ክቡር ኡሁሩ ኬንያታ የሚመሩትና ከ37 የአፍሪካ ሀገሮች የተወጣጡ 83 ታዛቢዎችን ያቀፈው የአፍሪካ ኅብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን ምርጫውን “ዴሞክራሲያዊ አስተዳደርን በሰፊው በሚደግፍ ሕጋዊና ተቋማዊ ማዕቀፍ ውስጥ የተካሄደ” ሲል ገምግሞታል። በቀድሞዋ የኡጋንዳ ምክትል ፕሬዚዳንት ክብርት ዶክተር ስፔሲዮዛ ዋንዲራ ካዚብዌ የሚመራው የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ቡድን ባወጣው የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት፥ በታዘቡባቸው ጣቢያዎች ሁሉ የምርጫ ሳጥኖች በትክክል የታሸጉ መሆናቸውን፣ የፓርቲ ወኪሎች በሂደቱ በሙሉ መገኘታቸውን እንዲሁም ምርጫው አስደናቂ ተቋማዊ፣ አስተዳደራዊና የቴክኖሎጂ ዕድገትን ያሳየ መሆኑን አረጋግጧል። የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ልዑክ ይሄንን ምርጫ «የበርካታ አዳዲስ ምዕራፎች ምርጫ» ሲል ሰይሞታል። የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በድምፅ መስጠት ሂደት ውስጥ ምንም ዓይነት የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳልተመለከተ አረጋግጧል። የሲቪክ ማኅበረሰብ ታዛቢዎች ጥምረት በምርጫ ቦርድ እውቅና ከተሰጣቸው 55 ድርጅቶች 65,299 የታዛቢዎችን በመላ ሀገሪቱ ያሠማራ ሲሆን፥ 99 በመቶ የምርጫ ጣቢያዎች ላይ ያለምንም ዕንቅፋት የመታዘብ ዕድል ማግኘቱን አረጋግጧል። እነዚህ ተዓማኒነት ያላቸው ሀገራዊ እና አኅጉራዊ ተቋማት ያደረጓቸው ግምገማዎችና የሰጧቸው እውነተኛ ፍርዶች ናቸው። እነዚህ ለአፍሪካ ጥላቻ ካላቸው ወይም የአፍሪካን ዴሞክራሲ በውጫዊ መሥፈርቶች ከሚለኩ ተቋማት የተደመጡ ድምፆች አይደሉም።
አንዳንድ ዓለም አቀፍ ተንታኞች ይሄንን ምርጫ እንደ ንግሥና በዓል አድርገው ያቆሸሹት ሲሆን ውጤቱም አስቀድሞ የተወሰነ ድራማ እንደነበር አድርገው ሊያቀርቡት ሞክረዋል። እነዚህን መግለጫዎች ከእውነታው ፈጽሞ የራቁ፣ በጥናትና ትንተና ላይ ያልተመሰረቱ እንዲሁም ነፃና የታሰበበት ዴሞክራሲያዊ ምርጫቸውን በኩራት ላደረጉ በሚልዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ክብር የማይሰጡ በመሆናቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሙሉ በሙሉ የማይቀበላቸው መሆኑን ያረጋግጣል። አስቀድሞ የተወሰነ ውጤት ቢኖር ኖሮ፤ ከ37 የአፍሪካ ሀገሮች የተወጣጡ 83 ገለልተኛ ታዛቢዎችን፣ 65,299 የሀገር ውስጥ የሲቪል ማኅበረሰብ ታዛቢዎችን ወይም 1,100 ዕውቅና የተሰጣቸውን ዓለም አቀፍ ጋዜጠኞች መጋበዝ ባላስፈለገ ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በዚህ ሀገራዊ ምርጫ ለተሳተፉ የኢትዮጵያ ዜጎች፣ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እና ላሠማራቸው ከ350,000 በላይ ኃላፊዎች፣ ሂደቱን ለጠበቁት የጸጥታ ኃይሎች እንዲሁም ኢትዮጵያ ለዴሞክራሲ ግንባታ መጎልበት እና ለሂደቱ መሳካት ያላትን ቁርጠኝነት ላረጋገጡት የአፍሪካ እና ቀጣናዊ የታዛቢ ቡድኖች ምስጋናቸውን ያቀርባሉ!
ስለ ኢትዮጵያ ልማት
ኢትዮጵያውያን ግንቦት 24 2018 ዓ.ም ውሳኔያቸውን ሲያስቀምጡ፣ ሀገራቸውን በፍጹም የዴሞክራሲ ባህል ውስጥ ለማንበር ነው። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ባላት ጸጋ ልክ የሚያስፈልጋትን ሁለንተናዊ ልማት በፍጥነት እውን የማድረግ ባህል እንዲቀጥል ሕዝባችን ተናግሯል።
ባለፉት ዓመታት የታየው እውነት እንደሚያሳየን የኢፌዴሪ መንግሥት የተስፋ ቃል መንግሥት አልነበረም። ይልቁንም በተጨባጭ የሚታዩ ውጤቶች የተመዘገቡበት ውጤት ተኮር መንግሥት ሲሆን፤ እነዚህም ውጤቶች በግልጽ የሚታዩ ናቸው። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በ2017 በጀት ዓመት የ9.2 በመቶ ዕድገት ያስመዘገበ ሲሆን፥ ይሄም በዓለም ላይ ፈጣን ዕድገት ካስመዘገቡ ኢኮኖሚዎች አንዱ ያደርገዋል። ይሄንን መነቃቃት መሠረት በማድረግ በ2018 በጀት ዓመት የኢኮኖሚ ዕድገቱ 10.2 በመቶ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል። ዕድገቱ ግብርናን፣ ኢንዱስትሪንና የአገልግሎት ዘርፎችን በከፍተኛ ደረጃ ያካተተ ሰፊ መሠረት ያለው ቢሆንም፥ ከጊዜ ወደ ጊዜ ግን ኢንዱስትሪው ለዕድገቱ ዋነኛ አንቀሳቃሽ ኃይል ሆኖ እየመጣ ይገኛል። ይሄም መንግሥት ለማኑፋክቸሪንግ፣ ለኢንዱስትሪ ልማት፣ ለዕሴት ጭማሪና ለውጭ ገበያ ተኮር ምርቶች የሰጠውን ቀጣይነት ያለው ትኩረት ያሳያል።
እነዚህ ውጤቶች እንዲሁ ግምቶች ብቻ ሳይሆኑ፥ በጠቅላይ ሚኒስትሩ የ100 ቀናት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ሥርዓት አማካኝነት ክትትል የሚደረግባቸው የተጠያቂነትና የታቀደ አመራር ፍሬዎች ናቸው። አጠቃላይ የወጪ ንግድ ገቢ 20 ቢልዮን የአሜሪካ ዶላር ይደርሳል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፥ ይህም ከ2016 ዓ.ም. ወዲህ የ100 በመቶ ገደማ ጭማሪ አሳይቷል። የዋጋ ግሽበትም ወደ ታች ማሽቆልቆሉን በመቀጠል አሁን ላይ ወደ አንድ አሐዝ ደረጃ እየተቃረበ ይገኛል፤ ይሄም በቅርብ ዓመታት ውስጥ በቤተሰቦችና በንግዶች ላይ ከባድ ጫና ፈጥሮ ከነበረው ባለ ሁለት አሐዝ የዋጋ ግሽበት አንጻር ትልቅ መሻሻል ነው። ይህ ስኬት የተመዘገበው ዓለም አቀፍ የኃይል አቅርቦትና ሌሎች ስትራቴጂካዊ ቁሳቁሶችን ገበያ ያናጋው የመካከለኛው ምስራቅ ወቅታዊ ጂኦፖለቲካዊ ውጥረት ጨምሮ፣ ውጫዊ ጫናዎች በነበሩበት ወቅት ነው።
የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ከተጀመረ ወዲህ መንግሥት ከውጭ ምንጮች ምንም ዓይነት አዲስ የንግድ ብድር ስምምነት ያላደረገ ሲሆን፥ ይሄም የሀገሪቱን የብድር ዕዳ ጫና በከፍተኛ ሁኔታ አቅልሎታል። ከእነዚህ ቁጥሮች በስተጀርባ ኢትዮጵያውያን በዓይናቸው የሚያዩትና በእጃቸው የሚዳስሱት ተጨባጭ ለውጥ አለ። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለመኖሪያ ቤቶች፣ ለንግድ ተቋማትና ለጎረቤት ሀገራት የኤሌክትሪክ ኃይል እያመነጨ ይገኛል። ይህ ግድብ በራሳቸው በኢትዮጵያውያን የተደገፈ፣ በኢትዮጵያውያን መሐንዲሶች የተገነባና ቀጣይነት የነበረውን ውጫዊ ጫናዎችን ተቋቁሞ የተጠናቀቀ ነው። ከሃይድሮ ፓወር ጎን ለጎን፥ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የሚገኘውን የአይሻ ሁለት የንፋስ ኃይል ማመንጫ እና በአርሲ ዞን የሚገኘውን የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች፤ በመሳሰሉ ሥራዎች የታዳሽ ኃይል አቅርቦቷን እያሰፋች ሲሆን፥ ይህም የቀጣናዊ ኢነርጂ ትብብርን እያሳደገ የብሔራዊ ኃይል አቅርቦት መረቡን የመቋቋም ዐቅም ያጠናክራል። በአፍሪካ አህጉር ታሪክ ውስጥ ትልቁ የመሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት አንዱ የሆነው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ ግንባታው ተጀምሯል። እነዚህ ምኞቶች አይደሉም፤ ተጨባጭ ሐቆች ናቸው።
ግብርና፣ አምራች ኢንደስትሪና ቴክኖሎጂ
በግብርናው ዘርፍ፣ የመንግሥት የምግብ ሉዓላዊነት አጀንዳ ወቅታዊ ለውጦችን ሳይሆን መዋቅራዊ ውጤቶችን እያስገኘ ቀጥሏል። በሶማሌ ክልል የጎዴ ዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካን ለመገንባት ከአሊኮ ዳንጎቴ ግሩፕ ጋር የተፈረመው አጋርነት የዘመኑ ጉልህ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንቶች አንዱ ማረጋገጫ ነው። ፋብሪካው በዓመት 3 ሚልዮን ሜትሪክ ቶን ዩሪያ የማምረት አቅም እንዲኖረው ታቅዶ እየተገነባ ሲሆን፥ ይሄም ኢትዮጵያን በዓለም ትላልቅ ማዳበሪያ አምራች ሀገራት ተርታ ያሰልፋታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም. የፕሮጀክቱን የግንባታ ሂደት በጎበኙበት ወቅት እንደገለጹት፤ “ይህ ፕሮጀክት በግብርና ትራንስፎርሜሽን፣ በምግብ ዋስትና፣ በኢንዱስትሪ ዕድገትና በኢኮኖሚ ራስን መቻል ላይ የተደረገ ስትራቴጂካዊ ኢንቨስትመንት ነው” ብለዋል። አስተማማኝ ባልሆነና ውድ በሆነ የማዳበሪያ አቅርቦት ለረጅም ጊዜ ለተገደቡት ኢትዮጵያውያን አምራቾች የዚህ ፕሮጀክት ፋይዳ ፈጣንና ተጨባጭ ነው።
ከዚህ ምርጫ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግንቦት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. በነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ ምርቃት ላይ ሲገኙ የታየው ተምሳሌትነት ለቦረና ሕዝብ ትልቅ ትርጉም ነበረው። ይህ ዞን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቅበት ስም የሀገርን አንገት ያስደፋ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትውስታ ሲሆን፤ እርሱም ድርቅ ነው። ለሦስት ተከታታይ ዓመታት የዝናብ መጥፋት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ከብቶችን የገደለ፣ ቤተሰቦች ለውኃ ፍለጋ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮችን እንዲጓዙ ያስገደደ፣ እንዲሁም በእነዚህ የግጦሽ መሬቶች ላይ ለዘመናት ራሳቸውን ችለው የኖሩ ማኅበረሰቦችን ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ እጅ እንዲዘረጉ አድርጎ ነበር። ዓለም የሚያውቃት ቦረና እርሷ ነበረች። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የግንቦት ወር ጉብኝት ግን የተለየ ታሪክ አሳይቷል። አሁን ላይ ለአርብቶ አደር ማኅበረሰቦችና ለከብቶቻቸው ንጹሕ ውኃ እያቀረቡ ያሉትን የውኃና የመስኖ መሠረተ ልማቶችን የገመገሙ ሲሆን፥ ከጥቂት ዓመታት በፊት አቧራ ብቻ በነበረው መሬት ላይ የክላስተር እርሻዎችን ጎብኝተዋል፤ በያቤሎ የባህል ማዕከል መርቀዋል፤ እንዲሁም በአየር ንብረት ሁኔታዎች ምክንያት ቀድሞ ተገልሎ ለነበረው ቀጣና ዓመቱን ሙሉ ትስስር የሚፈጥር አውሮፕላን ማረፊያ መርቀው ከፍተዋል።
የአምራች ዘርፉም ተመሳሳይ የለውጥ ታሪክ አለው። በግንቦት 2018 ዓ.ም. በተካሄደው 4ኛው ኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ላይ፤ መንግሥት ለአራት ዓመታት የተመዘገበውን ቀጣይነት ያለው የኢንዱስትሪ መስፋፋት ውጤቶች አቅርቧል። የአምራች ዘርፉ የግብአት አቅርቦት በዓመት 9 ሚልዮን ቶን ወደ 15 ሚልዮን ቶን አድጓል። የምርት አቅም አጠቃቀም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማለቱን፣ የማኑፋክቸሪንግ ዕድገት ከ4.8 በመቶ ወደ 10.7 በመቶ ማደጉን፣ እንዲሁም ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች የሚቀርበው ፋይናንስ ከ8.1 ቢልዮን ብር ወደ 50 ቢሊዮን ብር ማደጉን ያሳያል። እነዚህ ስኬቶች በሀገር ውስጥ ምርት ላይ በከፍተኛ ሁኔታ እየተንጸባረቁ ይገኛሉ። ኤክስፖው በተጠናቀቀ በሃያ ቀናት ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ ተጠናቆ ከ80 በመቶ በላይ ጥሬ ዕቃውን ከሀገር ውስጥ የሚያገኘውን ግዙፍ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት «ግራንዲዩር የሴራሚክ ማኑፋክቸሪንግ» ፋብሪካን በሞጆ ከተማ መርቀዋል። ቀደም ሲል በገቢ የሴራሚክ ምርቶች ላይ ጥገኛ የነበረችው ኢትዮጵያ አሁን ላይ የሴራሚክ ምርቶችን ከውጭ ማስገባት ሙሉ በሙሉ ለማቆምና ለውጭ ገበያ የሚሆን ምርት ለማስፋፋት እየተዘጋጀች ትገኛለች።
በቴክኖሎጂው ዘርፍም፥ ዘመናዊ ልማት ከጊዜ ወደ ጊዜ በዳታ፣ በፈጠራና በዲጂታል ሥርዓቶች የሚወሰን መሆኑን በመገንዘብ፥ መንግሥት ኢትዮጵያን ሰው ሠራሽ አስተውሎት እና የኢንዱስትሪ 5.0 ማሕቀፎችን ቀድመው ከተገበሩ ሀገራት ተርታ እያሰለፋት ይገኛል።
የጽንፈኝነትን ፖለቲካ ውድቅ ማድረግ
በኦነግ ሸኔ ዐማጽያን በንጹሐን ዜጎች ላይ በተለይም በሃይማኖት ተቋማት ውስጥ ዒላማ ተደርገው የተፈጸሙ ጥቃቶችን ተከትሎ፤ የቤተሰብ እና የወዳጆቻቸውን ሕይወት ላጡ፣ የአካል ጉዳት ለደረሰባቸው እና የቤት ንብረታቸው ለወደመባቸው በአርሲ ዞን ለሚገኙ ወገኖቻችን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በኢትዮጵያ መንግሥት ስም የተሰማቸውን ጥልቅ ኀዘን ይገልጻሉ።
እነዚህ ጥቃቶች የሀገሪቱን ብሔራዊ ዕድገት ለማደናቀፍ ከሚሹ አካላት፣ በአማራ ክልል ከሚንቀሳቀሱ የሀገር ውስጥ አማፂ ቡድኖች እና ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ጥላቻ ካላቸው የውጭ ኃይሎች ጋር በጥምረት የተከናወኑ ሲሆኑ፤ ዓላማቸውም በኢትዮጵያ አለመረጋጋትንና የምርጫ መስተጓጎልን ለመፍጠር ሲደረግ የነበረ የጥፋት ውጥን ተከታይ ነው። መንግሥት 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ያለ አንዳች የፀጥታ ችግር ፍትሐዊና አሳታፊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ልዩ ትኩረትና ዝግጅት በማድረግ በቁርጠኝነት ሲሠራ ቆይቷል። በሌላ በኩል የጥፋት ኃይሎች ከባዕዳን ጋር 'ፅምዶ' የሚል ቁርኝት በመፍጠር ዕኩይ ዓላማቸውን ለማሳካት ሰፊ የጥፋት ዝግጅት ሲያድርጉ ቆይተዋል፣ ሀገራዊ ምርጫው እንዳይከናወን ሰፊ ርብርብ አድርገዋል። በተጨባጭም በቅድመ ምርጫ እና በምርጫ ወቅት የዜጎችን የመምረጥ መብትና ነጻነት ለመጋፋትና ለማደናቀፍ አለን የሚሉትን የጥፋት እጅ ዘርግተዋል።
እነዚህ የጠላት ኃይሎች በመደጋገፍና በመናበብ ዐመፅና ሁከት ለማነሳሳት፣ ከተሞችን በሽብር ጥቃት ለማወክ፣ በመንገዶች የደፈጣ ጥቃት በመፈጸም እንቅስቃሴ ለመገደብ እና በተወሰኑ አካባቢዎች ዒላማ አድርገው ነጥሎ ለማጥቃት ተንቀሳቅሰዋል። እንደ ማሳያ የጦር መሣሪያ፣ ተተኳሾችንና ሌሎች ሎጀስቲክሶችን በድጋፍ በማቅረብ በደቡባዊ ትግራይ በሚገኙ አዋሳኝ የአማራ ክልል አንዳንድ ቦታዎች ላይ ትንኮሳ ፈጽመዋል፣ በአማራ ክልል ባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደብረ ብርሃን እና ወልድያ ከተሞችን ጨምሮ በክልሉ ዋና ዋና ከተሞች እና ሲቪሎች ላይ ዒላማ በማድረግ ያካሄደው የሽብር እንቅስቃሴና ዝግጅት፣ በአዲስ አበባ ከተማ ባደራጃቸው የኅቡዕ ሴሎች አማካኝነት በተመረጡ አከባቢዎች ላይ ጥቃት እንዲፈጸም ተንቀሳቅሰው የነበረ ቢሆንም ይሄን የጥፋት ሴራ እና ድርጊት እንዲከሽፍ ማድረግ ተችሏል።
በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል የሸኔ ሽብር ቡድን ከጽንፈኛው ፋኖ ታጣቂ ቡድን ጋር በመናበብ በአንዳንድ አካባቢዎች መንገዶችን በመዝጋት እንቅስቃሴ ለማስቆምና ለማስተጓጎል ፍላጎት የተንቀሳቀሰ ቢሆንም በጸጥታ ኃይሉ በተወሰደበት የተጠናከረ እርምጃ ፍላጎቱን ማሳካት አልቻለም። ቡድኑ በፀጥታ ኃይሉ የተወሰደበትን ርምጃ መቋቋም ባለመቻሉ እና ፍላጎቱን ማሳካት ባለመቻሉ ስስ ዒላማዎች ላይ ያተኮረ ርምጃ በመውሰድ የሃይማኖት እና የብሔር ግጭት ለመቀስቀስ በማለም በአርሲ ዞን አሰኮ እና አካባቢው ጥቃት በመፈጸም ሁሉን አይነት የጥፋት ርብርብ ያደረገ ቢሆንም ሁኔታውን በመቆጣጠር ፀጥታ ኃይላችን በእነዚህ ኃይሎች ላይ የተቀናጀ ርምጃ እየወሰደ ይገኛል።
መንግሥት መሰል ሥጋቶችን በንቃት በመከታተል ላይ ሲሆን፣ በምርጫው ወቅትም በብዙ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተቀነባበሩ ተመሳሳይ ዕቅዶችን በስኬት ማክሸፍ ችሏል። በንጹሐን ዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን፤ ፍርሃትና ክፍፍልን ከሚያጎሉ የሚዲያ ዘመቻዎች ጋር በማስተሣሠር የተቀነባበረው ይህ እኩይ ተግባር፤ በመንግሥት የደኅንነት መዋቅርና ኦፕሬሽኖች አማካኝነት በከፍተኛ ሁኔታ እንዲስተጓጎል ተደርጓል። ብሔራዊ እና ሃይማኖታዊ ክፍፍልን ለመዝራት የኃይል ጥቃትን እና ውድመትን እንደ መሣሪያ የሚጠቀሙ አካላት በሁሉም ኢትዮጵያውያን ዘንድ በግልጽ ሊወገዙ ይገባል። መሰል ተግባሮች በኢትዮጵያ ውስጥ ምንም ዓይነት የወደፊት ዕድል እንደሌላቸው ለማሳየት የተቀናጀ ብሔራዊ ምላሽ በመስጠት ወሳኝ ርምጃዎችን ይቀጥላል።
በንጹሐን ዜጎች ላይ ጥቃት የሚፈጽሙ አካላት፣ ድርጊታቸውን ምክንያታዊ ለማስመሰል ምንም ዓይነት የፖለቲካ ንግግር ቢጠቀሙ፤ ወሳኝ ዓላማን እያሳኩ ሳይሆን ወንጀል እየፈጸሙ ነው። የፖለቲካ ቅሬታዎች በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት፣ በብሔራዊ ምክክር ሂደት እና በዴሞክራሲያዊ ተቋማት አማካኝነት መፍትሔ ሊያገኙ የሚችሉ እና ሊያገኙ የሚገባቸው ናቸው።
ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም!
05/06/2026
ከንቲባ አዳነች አቤቤ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ያደረጉት በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነው የዳግማዊ ምኒሊክ ሆስፒታል ዘመናዊ የፎረንሲክ (ዲ ኤን ኤ) እና የሥነ ምረዛ ምርመራ ልሕቀት ማዕከል ምረቃ ሥነ ሥርዓት በምስል
05/06/2026
ዛሬ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነ፣ የሕዝባችንን የጤና አገልግሎት በአዲስ ከፍታ ላይ የሚያስቀምጥ አዲስ የዲኤንኤ(DNA)፣ የፎሬንሲክና ስነምረዛ ምርመራ የልህቀት ማዕከል መርቀን ለአገልግሎት ክፍት አድርገናል።
ሀገራችን ብዙ የውጭ ምንዛሪ የምታጣበት እና የምርመራ ውጤት ለማግኘት በጣም ረጅም ጊዜ ይፈጅ የነበረውን ችግር የሚያስቀር የDNA መረጃ ማከማቻና ማነጻጸሪያ ሲስተም (CODIS)፣ በወንጀል የተጠረጠሩ፣ ወላጅነትን ለማረጋገጥና ተመሳሳይ ምርመራዎችን በዘር መለያ (DNA Profiling) ለመለየት፣ የቤተሰብ ግንኙነትን እስከ ዘር ሀረግ መለየትና ማረጋገጥ እንዲሁም አጠራጣሪ ማንነትን ለማወቅ የሚያስችል የልህቀት ማዕከል ነው።
ይህ ማዕከል የሀገሪቱን የፍትሕ ሥርዓት ምርመራን ውጤታማ በማድረግና በማዘመን፣ በሳይንሳዊ ማስረጃ ላይ የተመሰረተ የወንጀል ምርመራ ለማካሄድ፣ የመብት ጥያቄዎችን ለመመለስና ለሕዝብ ጤና ጥበቃ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ብሔራዊ የልህቀት ማዕከል ነው።
ሁሌም ቃልን በተግባር ፈፅመን በቁርጠኝነትና በተሻሻለ የስራ ባህል እየሰራን ባለፉት 5 ዓመታት ለጤናው ዘርፍ ልዩ ትኩረት በመስጠት 4 ዓለም አቀፍ ደረጃ የሚመጥኑ ሆስፒታሎች በመገንባትና ነባሮቹንም ሆስፒታሎች በማደስና በማስፋፋት ሰፊ ስራዎችን ሰርተን አዘምነናቸዋል፡፡
በከተማ አስተዳደራችን በጤናው ዘርፍ የኢትዮጵያን የዕድገት ተምሳሌትነት እና የከፍተኛ ቴክኖሎጂ ምዕራፍ እያበሰርን ነው! ተጠናክሮም ይቀጥላል።
ከዚሁ ጎን ለጎን የጤና ባለሙያዎቻችንን ትጋት፣ ብቃት እና እምነት ይበልጥ ለማሳደግ ልዩ ትኩረት እንሰጣለን።
ከእቅድ ጀምሮ የልህቀት ማዕከሉ እውን እንዲሆን አስተዋጽኦ ያደረጋችሁትን በሙሉ በራሴ፣ በከተማ አስተዳደሩ እና በተጠቃሚዎች ስም ከልብ አመሰግናለሁ።
ፈጣሪ ኢትዮጵያን እና ህዝቦቿን ይባርክ!
ከንቲባ አዳነች አቤቤ
05/06/2026
አዲስ አበባን የአፍሪካ የከተሞች ልማት ተምሳሌት ያደረገው የ24/7 የመፈጸም አቅም
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጥቅምት 12 ቀን 2016 ዓ.ም "የዛሬ አምስት ዓመት አዲስ አበባ በአፍሪካ ውስጥ እጅግ ውብ ከሚባሉ ከተሞች አንዷ ትሆናለች" በማለት አቅጣጫ ያስቀመጡት ከተማዋ ስሟን የምትመጥን እንድትሆን በማሰብ ነው።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል ዛሬ በከተማዋ ተግባራዊ በሆኑት መዋቅራዊ እና ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች አማካኝነት በተጨባጭ እውን እየሆነ ይገኛል።
ይህንን ታላቅ ሀገራዊ ራዕይ ወደ መሬት አውርዶ በተግባር ለመተርጎም ደግሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያሳየው የአፈጻጸም ብቃት ሁነኛ ሚና ተጫውቷል።
በከንቲባ አዳነች አቤቤ የሚመራው የከተማዋ አመራር ቁርጠኝነት የለውጡ ዋነኛ አንቀሳቃሽ ሞተር ሆኖ አዲስ አበባን እንደ ስሟ የፈካች አበባ አድርጓታል።
አስተዳደሩ ያሰፈነው የ24/7 (ቀን ከሌሊት) የሥራ ባህል ቀደም ሲል ለዘመናት ስር ሰድዶ የነበረውን ዝግተኛ የመንግሥት ቢሮክራሲ በመስበር፣ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ እና በከፍተኛ ጥራት የማጠናቀቅ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ከፍቷል።
ይህ የሥራ ባህል ለውጥ ከተማዋን የማዘመን ተግባር ብቻ ሳይሆን፣ የከተማዋን ኢኮኖሚ ሌት ተቀን በማንቀሳቀስ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል የፈጠረ የልማት ኃይል ሆኖ እያገለገለ ይገኛል።
የአመራሩ በቢሮ ከመቀመጥ ይልቅ በምሽት የሥራ እንቅስቃሴዎች ላይ በአካል በመገኘት እና በመከታተል፣ በበዓላት ቀናት ከኮሪደር ልማት ሠራተኞች ጋር ማዕድ በመጋራት፣ እንዲሁም ሠራተኛውን በቅርበት በማበረታታት መሪነትን በተግባር አሳይተዋል።
ይህ ዓይነቱ ያልተቋረጠ የአመራር ክትትል እና አብሮነት የሥራ ባህልን በመቀየር ረገድ ትልቅ ሥነ-ልቦናዊ ለውጥ አምጥቷል።
የአስተዳደሩ ትጋት ከተማዋ ላይ ያመጣቸው ተጨባጭ ለውጦች ያፈሩት ፍሬ ዛሬ በገሃድ ይታያል፤ በርካቶችንም ተጠቃሚ አድርገዋል።
የከተማዋን ገጽታ ሙሉ ለሙሉ የቀየሩት ሰፋፊ የኮሪደር ልማቶች፣ ግዙፉ የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ የአዲስ አበባ ኢንተርናሽናል ኮንቬንሽን ሴንተር፣ የወንዝ ዳር ልማቶች፣ ማራኪ የሆኑት የሕዝብ መዝናኛ ስፍራዎች እና ዘመናዊ የመንገድ መሰረተ ልማቶች የአዲስ አበባን ትክክለኛ ውበት አጉልተው አውጥተውታል።
አዲስ አበባን የኪነ ጥበብ እና ፍልስፍና ማዕከል ለማድረግም ዘመናዊ የሲኒማ ኮምፕሌክሶች እና አምፊ ቴአትሮች በስፋት ተሠርተው ለአገልግሎት በቅተዋል።
አዲስ አበባ መጪውን ጊዜ ስታስብ ትላንቷንም ሳትረሳ ኢትዮጵያን ላገለገሉት ልጆቿ መታሰቢያ በማቆም ለቅርሶቿ ጥበቃ አድርጋለች።
የወንዝ ዳር ልማት፣ ትላንት የበሽታ እና የወንጀል ምንጮች የነበሩ ወንዞችን በማደስ ለከተማዋ አዲስ አስትንፋስ ሰጥቷል።
እነዚህ ተከታታይ ስኬቶች አዲስ አበባ ስሟን የሚመጥን ከተማ እንድትሆን ከማድረጋቸውም ባሻገር፣ የአፍሪካ ኅብረት መቀመጫነቷን እና የዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን በሚመጥን መልኩ የዓለምን ቀልብ በከፍተኛ ሁኔታ እንድትስብ አድርጓታል።
ዛሬ ላይ ቱሪስቶችም ሆኑ ዓለም አቀፍ ልዑካን በከተማዋ ንጽህና እና ፈጣን ዕድገት መገረማቸውን በተደጋጋሚ ከመግለጽ አልፈው በአካል መጥተው ለዓለም አረጋግጠዋል።
መዲናችንን የጎበኙ ዓለም አቀፍ ተፅዕኖ ፈጣሪዎችም ከተማዋ ከየትኛውም የዓለማችን ከተማ ጋር የምትወዳደር ውብ ከተማ እንደሆነች አረጋግጠዋል።
ከዚህም በላይ የከተማ አስተዳደሩ የጀመረው የኮሪደር ልማት እና የመልሶ ማልማት ሥራ፣ ማንንም ወደ ኋላ የማይተው ሰው-ተኮር መርሕን የተከተለ መሆኑ ልዩ ያደርገዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያስመዘገበው ይህ አስደናቂ የመፈጸም አቅም እና የልማት አርአያነት በዋና ከተማዋ ብቻ ተወስኖ አልቀረም።
ከተማ አስተዳደሩ ይህን ተጨባጭ ለውጥ ወደ ክልል ከተሞችም በተሳካ ሁኔታ እንዲሰርጽ አድርጓል።
ባለሙያዎችን በመመደብ እና የቴክኒክ ድጋፎችን በማቅረብ ታሪካዊቷ የጎንደር ከተማ የጀመረችውን የኮሪደር ልማት በፍጥነት እና በጥራት እንድታከናውን ትልቅ አሻራውን አሳርፏል።
በተመሳሳይ መልኩ የሐይቆች ከተማ የሆነችውን ቢሾፍቱ ከተማን የኮሪደር ልማት እና የቱሪስት መዳረሻነት ለማጠናከር የተደረጉት የልምድ ልውውጦች፣ የአመራሩን አጋርነት እና ሀገራዊ ቁርጠኝነት በተግባር ያሳዩ ናቸው።
በአዲስ አበባ የታየው ይህ አስደናቂ ለውጥ በምኞት የመጣ ሳይሆን፣ በጠንካራ መዋቅራዊ ዕቅድ፣ ቀን ከሌሊት በሚተጋ ቁርጠኛ አመራር፣ በተለወጠ የሥራ ባህል እና ከሕዝብ ጋር በተመሠረተ ጠንካራ ትሥሥር የመጣ ውጤት ነው።
ይህ ስኬት "የጀመርነውን እናጠናቅቃለን" የሚለውን የይቻላል መንፈስ በዜጎች ልቦና ውስጥ ያሰረጸ እና መላው ኢትዮጵያውያን በመዲናቸው እንዲኮሩ ያደረገ ብሩህ ተስፋ ነው።
አዲስ አበባ ዛሬ በአፍሪካ እጅግ ተወዳዳሪ፣ ለነዋሪዎቿ ምቹ እና ለሌሎች ከተሞች ታላቅ የልማት ትምህርት ቤት ሆና በኩራት ቆማለች።
EBC
05/06/2026
በጀት ዓመቱ ከመጠናቀቁ በፊት 3 የመሶብ ዲጂታል አንድ ማዕከላት ተጠናቀው ለአገልግሎት ዝግጁ ይሆናሉ - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ በይፋ የመረቁት የመሶብ ዲጂታል አንድ ማዕከል ነዋሪዎችን ለዓመታት ሲያማርር ከኖረው የአገልግሎት አሰጣጥ እንግልትና ከብልሹ አሠራር የሚታደግ መሆኑን ገልጸዋል።
ከንቲባ አዳነች በማዕከሉ የምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የኮልፌ ነዋሪዎችን ከአገልግሎት አሰጣጥ እንግልትና ከሙስና የሚታደገው የመሶብ ዲጂታል ማዕከል በይፋ ሥራ መጀመሩን አብስረዋል።
ይህ ዘመናዊ የዲጂታል ማዕከል ለአንድ ወቅት ብቻ ሳይሆን ፣ የረጅም ጊዜ የሀገር ግንባታን ታሳቢ ባደረገ መልኩ የተገነባ መሆኑን የጠቆሙት ከንቲባዋ፤ ነዋሪዎች በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚደርስባቸውን ውጣ ውረድ በማስቀረት፣ ጊዜያቸውንና ገንዘባቸውን ሳያባክኑ የፈለጉትን አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል።
በከተማዋ በርካታ የልማት ሥራዎች ቢሠሩም፣ አሁንም ድረስ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ የሚታዩትን እንደ ፈጣን አገልግሎት አለመስጠት፣ እንግልት እና የእጅ መንሻ (ጉቦ) ጥያቄዎችን ከመዋቅሩ ውስጥ መንጭቆ ለማውጣት ማዕከሉ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል።
ነዋሪዎች ፈጣን፣ ቀልጣፋና ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ያለምንም ጉቦ ማግኘት የሚችሉበትን አስተማማኝ ሥርዓት ይፈጥራል ብለዋል ከንቲባ አዳነች።
በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ የተጀመረው ይህ የዲጂታላይዜሽን ንቅናቄ በዚህ ብቻ እንደማያበቃ የገለጹት ከንቲባ አዳነች ፣ ሦስት ተመሳሳይ የዲጂታል ማዕከላት የበጀት ዓመቱ ከመጠናቀቁ በፊት፣ ተጠናቀው ለሕዝብ አገልግሎት ክፍት እንደሚሆኑ አስታውቀዋል።
ሕዝቡ በምርጫው ወቅት ያሳየው ታላቅ ፅናትና ፍላጎት፤ ሰላም፣ ልማት እና አጠቃላይ ሀገራዊ አካሄዶች በሕጋዊ መንገድ ብቻ እንዲጓዙ መሻቱን በተግባር ያረጋገጠበት መሆኑን ገልጸዋል።
በመሆኑም የዚህን ፅኑ ሕዝብ ጥያቄዎችና ፍላጎቶች በሚመጥን መልኩ ምላሽ መስጠት፣ ሥልጣን ከሚይዘው አካል የሚጠበቅ ኃላፊነት መሆኑን አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ ያለምንም የውጭ ተፅዕኖ 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ በራሷ ሕዝቦች፣ በሰላማዊና በዲሞክራሲያዊ መንገድ ማካሄዷ እና በምርጫው ማግስትም እንደነዚህ ያሉ ተጨባጭ ፍሬዎችን ማስመዝገቧ፣ የጀመረችው የብልጽግና ጉዞ ወደ ከፍታ እንደሚመራ ትልቅ ተስፋ የሚሰጥ ማሳያ መሆኑን ከንቲባዋ ገልጸዋል።
05/06/2026
በቀድሞው የአዲስ አበባ ከንቲባ አምባሳደር አሊ አብዶ ህልፈተ ህይወት ጥልቅ ሃዘን ተሰምቶኛል።
አምባሳደር አሊ አብዶ 27ኛ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ በመሆን እንዲሁም በሱዳን እና በናይጄሪያ የኢትዮጵያ አምባሳደር በመሆን ሀገራቸውን ያገለገሉ የሃገር ባለውለታ ናቸው።
ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጆቻቸው እና ለመላው ህዝብ መጽናናትን እመኛለሁ።
ፈጣሪ ነብሳቸውን በአጸደ ገነት ያኑር።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ