09/11/2025
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጠቅላይ ቤተ ክህነት በሕግ አገልግሎት መምሪያ የሕግ ባለሙያዎች ዐብይ ኮሚቴ መንፈሳዊ ጉባኤና ምክክር መርሐ ግብር ብፁአን አባቶች በተገኙበት አከናወነ::
የሕግ ባለሙያዎች ዐብይ ኮሚቴ ከተጣለበት ኃላፊነት ጎን ለጎን መንፈሳዊ ጉባኤ በማዘጋጀት የአባላቱን ሁለንተናዊ መንፈሳዊ ሕይወት በስብከተ ወንጌል ለማነፅ ይቻል ዘንድ በ2 ወር አንድ ጊዜ መርሐ ግብር ያዘጋጃል::
በዕለተ ቅዳሜ ጥቅምት 28 ቀን 2018 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽርሐ ተዋሕዶ አዳራሽ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ, ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የሚኒሶታና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ, ብፁዕ አቡነ ዲሜጥሮስ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ, ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት, የመምሪያው ኃላፊ አፈ መምህር አባ ገብረሥላሴ ጌትነት እና መምህራነ ወንጌል በተገኙበት ተከናውኗል::
የዕለቱን ትምህርተ ወንጌል ዲን ያረጋል አበጋዝ ያስተማሩ ሲሆን ዘማሪት ሲስተር ፋሲካ በዝማሬ አገልግለዋል::
በዕለቱም በተደረገ ወቅታዊ ምክክር የአርሲ ሀገረ ስብከትን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ስፍራዎች በቤተ ክርስቲያኒቱ , በአገልጋይ ካህናትና ምዕመናን ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን በተመለከተ ምክክር የተደረገ ሲሆን እንዲህ አይነት ድርጊቶችን በተመለከተ ከወትሮው በተለየ ሁኔታ የሰብዓዊ መብት ማስከበር ሥራን በልዩነት የሚሠራ ግብረ ኃይል እንዲዋቀርና ለተግባራዊነቱም ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስትያናችን እንዲሁም መንግስታዊ አካላት ጋር በቅርበት በመሥራት ለውጤት ለመትጋት ኃላፊነት ተወስዷል::
በተጨማሪም በዕለቱ የተገኙት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ "ከመቼውም ጊዜ በላይ ይህ የሕግ ባለሙያዎች ስብስብ ለቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎት አስፈላጊ መሆኑን በመግለፅ በቀጣይነትም በጋራ በመሥራት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁለንተናዊ መብትና ጥቅም ለማስጠበቅ እንደሚተጉ" ገልፀው አባታዊ ቡራኬና ቃለ ምዕዳን ሰጥተው መርሐ ግብሩ ተጠናቋል::

07/11/2025
30/10/2025
21/10/2025
29/09/2025