በፕላን የምመራ ከተማ ማድረግ
የከተማ መሬት አስተዳደር ስርዓቱን በማዘመን ውስን የሆነውን ሀብታችንን ለላቀ ልማት እናውል
የመሬት ፓሊሲያችን በገጠርም ሆነ በከተማ መሬት የመንግሥት እና የሕዝብ ሆኖ የከተማ መሬትን ተከራይቶ ለተወሰነ ጊዜ የመጠቀም መብትን ያረጋግጣል፡፡
በዚህ መሠረት መሬት የመንግሥትና የሕዝብ በመሆኑ ለሕዝብ ጥቅም ተፈላጊ የሆነውን መሬት መንግሥት በእጁ በማቆየት ጥቅም ላይ እንዲያውል በተጠቃሚዎች የተያዘ ከሆነም ተጠቃሚዎች በማሳመን፣ተገቢውን የንብረት ካሣ በመክፈል የተሻለ ልማት እንዲሰራበት ያደርጋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የከተማ ልማት ፓሊሲው የመሬትንና የቤት ዋጋን ለማረጋጋት እንዲሁም በፍትሐዊ መንገድ ልማታችን በሚያስቀጥልና የህዝብ ተ
ጠቃሚነት ባረጋገጠ አግባብ ለማቅረብ እንደሚያስችል ያስቀምጣል፡፡ የከተማ መሬትን በተመጣጣኝ ዋጋና በረጅም ጊዜ ክፍያ ለተጠቃሚዎች ማከራየት ተጠቃሚው መሬት ለመግዛት በአንዴ ብዙ ገንዘብ ወጪ እንዳያደርግና በዚህ ሂደትም የሚያድነውን ገንዘብ ለሌላ ልማት ለማዋል እንዲችል ይረዳል፡፡
መሬትን ዘመናዊ በሆነ አመራር ዘዴ በቁጠባ ለተለያዩ አገልግሎት ለማዋል የተለያየ መርሆች መከተል አስፈላጊ ነው፡፡ የከተማ መሬት በጣም ቁልፍ ግን ውሱን ሀብት በመሆኑ በመሬት አጠቃቀም ፕላን መሠረትና በቁጠባ መጠቀም ይኖርብናል፡፡ ስለሆነም የከተማ መሬትን በከተማ ኘላን መሠረት ለተፈላጊው አገልግሎት በቅደም ተከተል መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡ የመሬት አቅርቦት በቅድሚያ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ልማትን በሚያፋጥንና በተረጋጋ ዋጋ፣ በቀጣይና ቀልጣፋ የአቅርቦት ሥርዓት መፈፀም አስፈላጊ ነው፡፡
የቤቶችና የሠፈሮችን መተፋፈግ የሚያስወግድ እንዲሁም ለመኖሪያ፣ ለሥራና ለመዝናኛ የሚሆን ቦታ አመጣጥኖና አቀናጅቶ ማቅረብ፣ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ነዋሪዎች በተመጣጣኝ ዋጋ ለመኖሪያና ለመስሪያ የሚሆን በቂ መሬት የሚያገኙበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ባለሃብቶች የመኖሪያና የመሥሪያ ቤቶችን ሰርተው በኪራይም ይሁን በሽያጭ እንዲያቀርቡ መሬት በተቀላጠፈና ቀጣይነት ባለው፣ ግልጸኝነትና ተጠያቂነት በሚያሰፍን መንገድ በጨረታ እንዲያገኙ ማድረግ፣የመሬትና የቤት አጠቃቀሙንም ጨምሮ ምዝገባ እንዲሁም የባለቤትነት ማረጋገጫና የንብረት ግብይት ሥርዓት መፍጠር፣ ለመኖሪያና ለመሥሪያ ቦታ የሚቀርብ መሬት በቅድሚያ በተቀናጀ መንገድ መሠረተ ልማት የተሟላለት እንዲሆን ማድረግ የመሬት አቅርቦት መርህ ውስጥ ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
የከተማ መሬት ዓይነትና መጠን፣ የሚገኝበት አካባቢ፣ ለምን አገልግሎት እንደሚውል በጥናት በመለየት በአብዛኛው በጨረታ እንዲሁም በምደባ ቀጣይነት ባለው መልኩ ለተጠቃሚዎች ሊሰጥ ይገባል፡፡ የአጠቃቀሙና የአሰጣጡ ቅደም ተከተልም እንደሚተከለው መሆን ይኖርበታል፡፡በመጀመሪያ ደረጃ ለኢንዱስትሪ፣ ለጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ለማምረቻና መሸጫ፣ ከዚያ በመቀጠል ለቁጠባ ቤቶች ቅድሚያ በመስጠት ከዚያም ለሌሎችም መኖሪያ ቤቶች ማዋል ነው፡፡ በአራተኛ ደረጃ ለማህበራዊ እና ለኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች፣ አምስተኛ ላይ ለሌሎች የንግድ ተቋሞች እና ለመዝናኛ ቦታዎች ታሳቢ ያደረገ ቅደም ተከተል መሰጠት አለበት፡፡
ቅደም ተከተሉ ከላይ እንደተገለጸው ሆኖ በየቀበሌውና በክፍለ-ከተማው ከኢንዱስትሪ አገልግሎቶች በስተቀር የሚዘጋጀውን ቦታ በማሰባጠርና አመጣጥኖ በመደልደል መፈጸም የሚገባ ሲሆን ከከተማው ኘላንና የመሬት ድልድል ጋርም መጣጣም ይኖርበታል፡፡ በተለይም የቁጠባ ቤቶችንና ሌሎች ቤቶችን እንዲሁም የመኖሪያና የሥራ ቦታን ያቀላቀለ፣ በየአካባቢው በቂ አረንጓዴና ለሕዝብ መዝናኛ አገልግሎት የሚውል ቦታ እንዲኖር የሚያስችል መሆንም አለበት፡፡
በአጠቃላይ ሀገራችን ካላት ሀብት አንዱና ዋነኛው መሬት በመሆኑ የመሬት አስተዳደር ስርዓቱን በማዘመንና ውስን የሆነውን ሀብታችንን በአግባበቡ በመጠቀም ለላቀ ልማት ማዋል አስፈላጊ ነው፡፡