07/05/2026
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሠራተኞች የሥራ ኃላፊዎች የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖን ጎበኙ
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሠራተኞች የሥራ ኃላፊዎች “ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት” በሚል መሪ ሐሳብ እየተካሄደ የሚገኘውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ጎብኝተዋል።
በኤክስፖው ላይ ለአካል ጉዳተኞች የአካል ድጋፍ ለማድረግ የሚያግዙ በኤሌክትሪክ የሚሠሩ ዊልቸርሮች፣ ለህፃናት ቅድመ ልጅነት ዕድገትን የሚያግዙ አገር በቀል የተመጣጠነ ምግብ አቅርቦቶችን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ አምራቾች ምርቶቻቸውን አቅርበዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው መክፈታቸው ይታወሳል።
07/05/2026
ባህል እየሆነ የመጣው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የህዝብ ለህዝብ ትስስርን፣ አብሮነትንና ሰላምን ከማጠናክር ባለፈ ዜጎች ለማህበረሰብ ለውጥና ለጠንካራ ሀገር ግንባታ በጎ አሻራቸውን እንዲያሳርፉ አስችሏል።
05/05/2026
በትግራይ ክልል "የወጣቶች ሰላምና ደህንነት ብሔራዊ የድርጊት መርሃ ግብር" ግብዓት ማሰባሰቢያ ወርክሾፕ ተካሄደ
************
(መቀሌ፣ ሰኞ ሚያዝያ 27/ 2018 ዓ.ም) በትግራይ ክልል ከመቀሌና አካባቢዋ የተወጣጡ ወጣቶች የተሳተፉበት "የወጣቶች ሰላምና ደህንነት ብሔራዊ የድርጊት መርሃ ግብር" ስትራቴጂክ ሰነድ ዝግጅት ላይ ያተኮረ ክልላዊ የምክክር ወርክሾፕ በዛሬው ዕለት ተካሂዷል።
መድረኩን በንግግር የከፈቱት የትግራይ ክልል የወጣቶች ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሃይሽ ስባጋድስ፣ የክልሉን ወቅታዊ ሁኔታና ከወጣቶች የሚጠበቀውን ሚና በተመለከተ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ኃላፊው በንግግራቸው፥"ትግራይ የኢትዮጵያ የማይነጠል አካል፣ ወጣቶቿም የኢትዮጵያ ወጣቶች ናቸው። በመሆኑም በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚወጡ ማናቸውም ፖሊሲዎችና የአሰራር ማዕቀፎች የትግራይን ነባራዊ ሁኔታና የወጣቶቿን ፍላጎት ያካተቱ መሆን አለባቸው" ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል።
በመቀጠልም በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የወጣቶች ማብቃት መሪ ስራ አስፈፃሚ ተወካይ አቶ አብዱለጢፍ ሙሃመድ በበኩላቸው፥ ሰነዱ በሀገር አቀፍ ደረጃ የወጣቶችን ሁለንተናዊ ደህንነትና የሰላም ግንባታ ተሳትፎ ለማረጋገጥ የታለመ መሆኑን ጠቁመው፣ ከትግራይ ወጣቶች የሚገኘው ግብዓት ለሰነዱ ጥራትና ተፈጻሚነት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።
በወርክሾፑ ላይ የተሳተፉት ወጣቶችም በቀረበው ሰነድ ላይ ጥልቅ ውይይት ያካሄዱ ሲሆን፣ በክልሉ ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ግምት ውስጥ ያስገቡ የተለያዩ ግብዓቶችን ሰጥተዋል።
በተለይም፦
• ወጣቶች በሰላም ግንባታ ሂደት ላይ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጎለብት፣
• የፖሊሲ ማዕቀፎች የክልሉን ወጣቶች ልዩ ፍላጎቶች እንዲያካትቱ፣
• እና የወጣቶች የኢኮኖሚና የማህበራዊ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ የሚሉ ነጥቦች በሰፊው ተነስተዋል።
ይህ መድረክ በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስተባባሪነት በየክልሎቹ የሚካሄዱ የምክክር መድረኮች አካል ሲሆን፣ ከመድረኩ የተገኙ ጠቃሚ ግብዓቶች ተጠቃለው በብሔራዊ ደረጃ በሚዘጋጀው ስትራቴጂክ ሰነድ ውስጥ እንደሚካተቱ ታውቋል።
መድረኩ የተዘጋጀው ሚኒስቴሩ ከክልሉ ወጣቶች ጉዳይ ቢሮ እና ከዩኤን ኤፍ ፒ(UNFPA) ጋር በመተባበር ነው።
05/05/2026
እንኳን ለ85ኛው የጀግኖች አርበኞች የድል በአል አደረሳችሁ!
04/05/2026
በሳዑዲ ዓረቢያ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ያሉ 1 ሺህ 546 ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው ተመለሱ
***************
(አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 26/ 2018 ዓ.ም) በሳዑዲ ዓረቢያ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ 1 ሺህ 546 ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል፡፡
በሳምንቱ ውስጥ በተደረገ 7 ዙር በረራ የተመለሱት 1ሺህ 237 ወንዶች እና 261 ሴቶች እንዲሁም 47 ጨቅላ ህፃናት ሲሆን ከተመላሾች መካከል 37 እድሜያቸው ከአስራ ስምንት አመት በታች የሆኑ ታዳጊዎች ይገኙበታል።
መስከረም 5/ 2018 በተጀመረው ዜጎችን ወደ ሀገር ቤት የመመለስ ስራ እስካሁን ከ68 ሺህ 700 በላይ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገር መመለስ ተችሏል።
ሚኒስቴሩ ለተመላሽ ዜጎች በአየር ማረፊያና በማቆያ ማዕከላት ተገቢውን ድጋፍ እና እንክብካቤ የማድረግ እና ከቤተሰብ ጋር የማቀላቀል ስራ ከሚመለከታቸው ባለድርሻና አጋር አካላት ጋር በመተባበር በትኩረት እየሰራ ይገኛል።
በተጨማሪም መደበኛ ባልሆነ ፍልሰት ወደ ተለያዩ ሀገራት ሄደው የሚመለሱ የፍልሰት ተጎጂዎችን ለመደገፍና መልሶ ለማቋቋም የሚያስችሉ ተግባራትን በትብብር እያከናወነ መሆኑ ይታወቃል።
ወደፊትም በህገወጥ የሰዎች ዝውውር አስከፊነት ዙሪያ ህብረተሰቡን ለማስገንዘብ፣ መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን ለመከላከልና ደህንነቱ የተጠበቀ ፍልሰትን ለማበረታታት ሚኒስቴሩ የጀመራቸውን ስራዎች አጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል።
**********
ስለ ሴቶችና ማሕበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት ከታች ያሉ ገፆቻችንን ይጎብኙ
For more information follow Ministry of Women and Social Affairs pages
*****
ድረ ገጽ፦ https://www.mowsa.gov.et/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/EthiopiaMoWSA
ቴሌግራም፦ https://t.me/MowsaEthiopia
ዩትዩብ፦ ministry of women and social affairs
03/05/2026
"ለሚመጣው ትውልድ ጽኑ፣ በኢንዱስትሪ የበለፀገች እና ራሷን የቻለች ኢትዮጵያን አንገነባለን!"
- ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ
03/05/2026
የኢፌዴሪ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ እየተከናወኑ ያሉትን የልማት ስራዎች ለመጎብኘት ቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ ገቡ
**************
የኢፌዴሪ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ እየተከናወኑ ያሉትን የልማት ስራዎች ለመጎብኘት ቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ ገብተዋል።
ክብርት ሚኒስትሯ ወደ ከተማ አስተዳደሩ ሲደርሱ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የብልፅግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቅሬ አማን፣ የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን፣ የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጅነር ሰለሞን ለዊን እና የከተማ አስተዳደሩ የብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ጊስካር ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የዞንና የከተማ አመራሮች ደማቅ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
የጉብኝቱ ዋና ዓላማ በዞኑና በከተማ አስተዳደሩ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ተግባራትን በአካል ተገኝተው ለመመልከትና ለመገምገም እንደሆነ ታውቋል።
ክብርት ሚኒስትሯ በቆይታቸው በተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ምልከታ የሚያካሂዱ ሲሆን ከዞኑ አመራሮች ጋርም የሥራ ውይይት እንደሚያደርጉ ይጠበቃል ሲል የዞኑ ኮሙዩኒኬሽን መረጃ ዘግቧል።
03/05/2026
በአማራ ብ/ክ/መንግስት በወጣቶች ሰላምና ደህንነት ብሔራዊ የድርጊት መርሃ ግብር የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረክ ተካሄደ
*****************
በታሪካዊቷ የጎንደር ከተማ የወጣቶችን የሰላም ግንባታ ሚና እና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ "የወጣቶች ሰላምና ደህንነት ብሔራዊ የድርጊት መርሃ ግብር" ስትራቴጂክ ሰነድ ዝግጅት ላይ ያተኮረ ክልላዊ የምክክር መድረክ ተካሂዷል።
በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እና በተባበሩት መንግሥታት የስነ -ሕዝብ ፈንድ (UNFPA) ትብብር በተዘጋጀው በዚህ መድረክ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የወጣት አደረጃጀት አመራሮች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ተወካዮች እና ወጣቶች ተገኝተው በሰነዱ ይዘትና ተፈጻሚነት ዙሪያ ሰፊ ውይይት አድርገዋል።
በመድረኩ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የአማራ ክልል ሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ብርቱካን ሲሳይ ወጣቱ የሀገር ግንባታና የለውጥ ዋነኛ ሞተር መሆኑን ገልጸዋል። ኃላፊዋ አክለውም ወጣቱ ሙሉ አቅሙን፣ ዕውቀቱንና ጉልበቱን ለዘላቂ ሰላምና ልማት ማዋል እንደሚገባው አሳስበዋል።
"የሀገር አደራ በወጣቱ እጅ ነው" ያሉት ወይዘሮ ብርቱካን ወጣቶች ካሉባቸው ዘርፈ ብዙ ችግሮች ተላቀው በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በንቃት እንዲሳተፉና የበኩላቸውን አበርክቶ እንዲያሳድጉ ጥሪ አቅርበዋል።
በመቀጠልም በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የወጣቶች ተሳትፎና የአደረጃጀቶች አቅም ግንባታ ዴስክ ኃላፊ አቶ አድነው አበራ ለውይይት መነሻ የሚሆን ጽሁፍ አቅርበው በተሳታፊዎች ሰፊ ምክክር ተደርጎበታል።
ይህ ስትራቴጂክ ሰነድ የወጣቶችን ድምፅ ለማካተትና መብታቸውን ለማስከበር ትልቅ ፋይዳ እንዳለው የተገለጸ ሲሆን ተሳታፊ ወጣቶችም እንዲህ ዓይነት መድረኮች ወጣቶች ለዘላቂና አዎንታዊ ሰላም ግንባታ የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት ለመወጣት አቅም እንደሚሆናቸው ገልጸዋል።
ከመድረኩ የተገኙ ጠቃሚ ግብዓቶች ተጠቃለው በብሔራዊ ደረጃ በሚዘጋጀው ሰነድ ውስጥ እንደሚካተቱ ተመላክቷል።
02/05/2026
በቅድመ ልጅነት ፕሮግራምና የህፃናት መንከባከቢያ ማዕከላት ማቋቋሚያ መስፈርትና አሰራር ዙርያ በሲዳማ ክልል የሚገኙ አስፈፃሚ አካላትን አቅም ለማጎልበት ያለመ ስልጠና ተሰጠ
**************
(ሐዋሳ፣ ሚያዝያ 24/2018 ዓ.ም) የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከክልሉ ሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ እና ከሴቭ ዘ ችልድረን (Save the Childern) ጋር በመተባበር በቅድመ ልጅነት ፕሮግራምና ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የአቅም ግንባታ ስልጠና ተሰጥቷል።
የሚኒስቴሩ የህጻናት መብትና ጥበቃ መሪ ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ዘቢደር ቦጋለ በመክፈቻ ንግግራቸው ከፅንስ ጀምሮ እስከ ስድስት አመት ያለው ጊዜ ከ90% በላይ የሰው ማንነት የሚቀረፅበት እድሜ ነው ብለዋል።
ይሁንና ባለፉት ዘመናት በማወቅም ሆነ ባለማወቅ በዚህ የእድሜ ክልል ውስጥ ላሉ ህፃናት ተገቢው ትኩረት ተሰጥቶ ባለመስራቱ ዛሬ ላይ ወጣቶች እና ታዳጊዎች ስብዕና ላይ ክፍተቶች መኖሩን ገልፀዋል።
በቅድመ ልጅነት ፕሮግራምና የህፃናት የቀን ማቆያና መንከባከብያ ላይ የሚሰሩ ስራዎች በሙሉ ቤተሰብን፣ ቀጣይ ሀገርን የሚያሻግሩና የተሟላ ስብዕና ያለው ትውልድን ለመፍጠር የሚረዳ መሆኑን ጠቁመዋል።
ማዕከላቱ ህፃናት ደህንነቱ የተጠበቀ አካባቢ ላይ እንዲውሉና የአይምሮ እድገት እንዲኖራቸው የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል።
ማዕከላቱ ከሚኖራቸው ፋይዳ አኳያ ማህበረሰቡን በማስተባበር በሁሉም የሀገሪቷ ክፍሎች ማስፋፋትና ተደራሽ ማድረግ ይገባል ብለዋል።
ስልጠናው በቅድመ ልጅነት ፕሮግራምና የህፃናት መንከባከቢያ ማዕከላት ማቋቋሚያ መስፈርት እና አሰራር ዙርያ በክልሉ የሚገኙ አስፈፃሚ አካላትን አቅም በማጎልበት በእውቀት ላይ የተመሠረተ ውጤታማ ስራ እንዲሰሩ ለማስቻል ያለመ እንደሆነ ገልፀዋል።
የክልሉ የሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ም/ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ፍጹም በላይ በበኩላቸው፥ የህፃት የቀን ማቆያና መንከባከቢያ ማዕከላት ህፃናት ብቻ ሳይሆን የሚጠቀሙት እናቶችም ለስራቸው ትኩረት እንዲሰጡ በተረጋጋ መንፈስ በተሰማሩበት የሰራ መስክ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ የሚያደርግ በመሆኑ ያገኙትን ግንዛቤ በስራ ላይ እንዲያውሉ አሳስበዋል።
በመድረኩ የህፃናት የቅድመ ልጅነት ዘመን ዕድገትና ትምህርት ፖሊሲ እና የማስፈፀሚያ ስትራቴጂ፣ የህፃናት መንከባከቢያና ማዕከላት ማቋቋሚያ መስፈርት እና አሰራርን ለመወሰን የወጣ መመሪያ 1084/2017 እንዲሁም በአዎንታዊ የህፃናት አስተዳደግ ዙሪያ እና የቀዳማይ ልጅነት እንክብካቤን መረዳትና የባለድርሻ አካላት ሚና ላይ ያተኮረ ሙያዊ ገለፃ ተደርጓል።
ሰልጣኞችም በተሰጣቸው ስልጠና ሰፊ ግንዛቤ እንደተፈጠረላቸው ገልፀው ቀጣይነት እንዲኖረው ጠይቀዋል።
በመርሐ ግብሩ ከሀዋሳ ከተማ አስተዳደር፣ ከዞንና ከወረዳ የተውጣጡ የጤና ቢሮ፣ የትምህርት ቢሮ፣ የከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ እንዲሁም የሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
30/04/2026
በሴቶች እና ማሕበራዊ ጉዳይ የተገኙ እመርታዎች: ‘እናት ሀገርን’ በተግባር መገንባት!
30/04/2026
የማህበረሰብ አቀፍ የህፃናት ማቆያና መንከባከቢያዎች መስፋፋት የሴቶችን ጫና በመቀነስ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ከማረጋገጥም ባለፈ ጤንነቱና ደህንነቱ የተጠበቀ ትውልድ ለመገንባት ትልቅ ሚና ይኖረዋል - ክብርት ሒክማ ከይረዲን
************
(ሐዋሳ፣ ሚያዝያ 22/2018 ዓ.ም) በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ አስተባባሪነት በPFC ገንዘብ ድጋፍ የተገነባው ማዕከል ምርቃትና ስራ ማስጀመርያ መርሀግብር ተካሂዷል።
የማህበረሰብ ዓቀፍ የቀን ማቆያና መንከባከቢያ ማዕከሉ የተገነባው በሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በሐዋሳ ከተማ ነው።
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የህፃናት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ሂክማ ከይረዲን የማህበረሰቡ የህፃናት መዋያና መንከባከብያ ማዕከል ትውልድ ለመገንባት፣ ትውልድ ለማነፅ፣ የተሻለ ትውልድ ለመፍጠር ትልቅ አስተዋፅዎ ያደርጋል ብለዋል።
የማህበረሰብ አቀፍ የህፃናት ማቆያና መንከባከቢያዎች መስፋፋት የሴቶችን ጫና በመቀነስ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ከማረጋገጥም ባለፈ ጤንነቱና ደህንነቱ የተጠበቀ ትውልድ ለመገንባት ትልቅ ሚና ይኖረዋል
ሚኒስቴሩ የህፃናትን መብት፣ ደህንነት፣ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ የተቀረፀውን የቅድመ ልጅነት ፖሊሲን ተግባራዊ ለማድረግ በቅንጅት እተስራ መሆኑን ገልጸዋል።
እንደሀገር 2ሺህ 500 የማህበረሰብ እና የተቋማት ዴኬር ተቋቁመው ከመቶ ሺ በላይ የሆኑ ህጻናትን ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል።
የቅድመ ልጅነት ፕሮግራም ሁሉን አቀፍ ፕሮግራሞችን አቀናጅቶ የያዘ ስለሆነ ተቀናጅተን ትውልድን እንገባ በማለት አስገንዝበዋል።
የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሃዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው ሀገራችን እንደ ፓርቲ ሰው ተኮር ስራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
የክልሉን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ በሚደረጉ ማናቸውም እንቅስቃሴዎች የክልሉ መንግስት በሩ ክፍት ነው ያሉ ሲሆን ይህንንም ስራ ለፍሬ ለማብቃት ከፌደራል እስከ ክልል ብሎም PFC አስተባባሪ አካላት ምስጋናን አቅርበዋል።
የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ እመቤት ኢሳያስ የነገዋን ሀገር የሚረከቡ ህፃናት መብትና ደህንነታቸው ተጠብቆ እንዲያድጉ በጋራ ልንሰራ ይገባል በማለት ተናግረዋል።
የማዕከል ምርቃትና ስራ ማስጀመርያ ላይ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የህፃናት ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች፣ የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ መምህራን እና የአካባቢው ኑዋሪዎች ተገኝተዋል።